ይህን አይልም መምህሩ !





ይህን አይልም መምህሩ !


፨   ፨    ፨   ፨   ፨

በዚህች፡ ፀሎተ፡ ጥሩምባ፡ አገር፡ በዚህች፡ የሱባኤ፡ ከበሮ፡ በሚንርባት፡ ምድር፣ በዚህች፡ በሰው፡ ልጆች፡ 
ስም፣ በዚህች፡ የካህናትና፡ የጠምጣሚ፡ መሲሀን፡ የፀሎት፡ ኡኡታ፡ ደወል፡ ከማንም፡ አገር፡ ጎልቶ፡ ንሮ፡ 
በሰው፡ ልጆች፡ በጎ፡ ስም፡ በሚያስገመግምባት፡ ምድር፡ ነው፤ የሰው፡ ልጆች፡ደም፣ ወዝና፣ ጉልበት፣ጎልቶና፣
ንሮ፡ሲፈስባት፡የምናየው። በዚህች፡የግዜር፡ ወኪል፣ የግዜር፡ ወሬ፡ ተርጓሚ፡ በዝቶ፡ በተጣበበት፡ አገር፡ 
ነው፡ ከየትም፡የትም፡ አገር፡ ይልቅ፡ የሰው፡ ወዝ፡ በከንቱ፡ ሲሽቀጥባት፡ የምናየው   
                                                                                                                                 
                                    ሎውሬት ፀጋዬ ገብረ መድህን፣ ከእናት ዓለም ጠኑ ትያትር የተወሰደ 
፨   ፨    ፨   ፨   ፨

ጠዋት ጠዋት ቀዳሹ
ቀን ቀን ተኳሹ
ጠዋት መምህሩ
ቀን ወታደሩ
ዕውቀት ከጠማው ሲጋተሩ 
ኧረ ለመሆኑ የዚህ መጻፉ ቃል
በዬትኛው ምዕራፍ በዬትኛው ወንጌል
ዝረፉ መዝብሩ ይላል?”

 ብሎ ሲጠይቅ

ሰውዬ  ምን ነክቶሀል?
እባክህ አትጃጃል
የባለጌ ሃይማኖት ከጅማት ይጠናል’’
ሲባል አልሰማህም? ጥንትም እኮ ይባላል
ብሎ ይሳለቃል።

***
እና እንዴት ነው ነገሩ?
አልገባኝም ምስጢሩ  
በእርግማን እያካለቡ
ወኔውን እየሰለቡ
ከሰማይ ታቦት እያዘነቡ
በየቦታው እያንጠባጠቡ
እኮ እንዴት? ባይን ፍርሀት እየመገቡ
ሰውን አርጎ ሆደ ቡቡ
በሰማይ እያሳበቡ   
በሱ ሥም እየማሉ
አንድ ነነ ብለው እያሉ
የተፈጠርነ  በአካሉ በአምሳሉ
በተቀባው ሥም  እየማሉ
እሱ የተከለውን ሲነቅሉ
ማንነቱን እየበከሉ
ንጥር እሴቱን እዬቀብሩ
ንጥር ባህሉን እዬመዘበሩ
ለጥበቡ  እንደመካስ
በደባትር ትንታግ ምላስ
የነግ ህይወቱን መላስ
ሥምና ግብሩን እያጣጣሉ
ይባስ ብለው ከመሰረቱ እየነቅሉ
ራስን በቦታው መትከሉ
ተጽፏል ወይ በወንጌሉ?
አስተምሯል ወይ መምህሩ?
ብሏል ወይ ይህን ተግብሩ?
አልገባኝም ምስጢሩ።

***
እሱ ግንክፋትን ከጥንቱ የገሰጸ
ሰላም ባጥንቱ የሰረጸ
ተቀበለ እንጅ አላመጸ
በቱውፊቱ ላይ ቱውፊት ቀረጸ
በባህሉ ላይ ባህል አነጸ
እንጂአልቀበልም አላለ
መቀበሉን በማተሙ እየማለ
ግን የሱን ፍቅር በቋንቋዬ ብሎ ባለ
የተቀባውስ ከዚህ ወድያ ምን አለ?
ሆኖም በሱ ቦታ ራሱን የወከለ፣
የለም! ብርሀነ ቃሉ የሚነገር
ቅዱስ ሥሙ የሚዘከር
ተአምሩ የሚወደስ የሚዘመር
በኔ ቋንቋ ካልሆነ በቀር
ከቶ አይሆንም የማይሆን ነገር !
ዘራፍ እምቡርርርር ! ጭራሽ እምቡርርርር !
እኮ ምን ሊፈይድ ነገር ማክረር?
መተግበሩ ጭራሽ ላይቀር!
ታድያ በተቀባው ስም እየማሉ
እሱን ከርስቱ እየነቀሉ
ራስን በይዞታው መትከሉ
ምን የሚሉት ፈሊጥ ነው በሉ?
መጽሀፉን ከጥግ ጥግ የሰለቅነ
በቃሉ ትርጉም የረቀቅነ
በግብረገብ የመጠቅነ
በረቂቃን ረቂቅነት የረቀቅነ
ከግዙፋን ግዙፍነት የገዘፍነ
አህዛብን ያሳመነ ያጠመቅነ
ሉሲፈርን ያዋረድነ ያበሸቅነ
ጥብሊያኮስን አካንኪኖስን
ጊናጦስን ዲያብሎስን
ጉግማንጉግዮስን ቅብጥርጥርዮስን
ምንትስዮስን ያበገነ ቀንድ ያስበቀልነ
ሚክአኤልን ገብርኤልን
ራጉኤልን ሩፋኤልን
ሱራፌልን ያመለክነ
በአረመኔ የተከበብነ
ብጹዕ ወ ቅዱሳን  ነነ።
ብለው ላለም ሁሉ ያሳበቁ
ታቦት ከሰማይ እያወደቁ
ጠበል ከጅረት እያፈለቁ
መሬት ከድሀ ሲነጥቁ
ጉድ ፈላ! አልነ አትስረቁን ሲሰርቁ
 
***
ያመነ ይድናል ሲሉት ያመነ ይድናል ብሎ
እግዚኦ በል ሲሉት እግዚኦ አድነነ ብሎ
ለነብስና ለስጋው ብርሀነ ቃሉን ተቀብሎ 
ታድያ ሰነባብቶ አድሮ ውሎ
ከቄዬውና ከማሳው ከነበረበት ተደላድሎ
ታቦት ወረደ  በጸበል ፈለቀ ተሸንግሎ
ሌላው በሱ መሬት ሲተከል እንዴት ይጣል ተነቅሎ?
ይህን ሁሉ መከራ ችሎ
ውሎ አድሮ አድሮ ውሎ 
ነገር ነገርን አብሰልስሎ
ለጊዜው ስንዱ መልስ ቢጠፋ
ውሎ አድሮ ግን ቅጥፈቱ ሲሆን ይፋ
ለኔ የዘነበው ታቦት ምነው ለነሱ አላካፋ?
ይህ ጸበል ከኔ ደጅ ካጋተ ከፈለቀ
ከሌላው ደጅ ምነው ነጠፈ ደረቀ?
ታቦት ከሰማይ ወድቆ
ጸበል ከደጄ ፈልቆ
አይነቅለኝም መሬቴን ነጥቆ 
ብሎ ቆርጦ ከእምነቱ ቢሸሽ
ማን ሊሆን ነው ተወቃሽ?

***
የአቻምናው ሹምባሽ
የትላንቱ  ቡሉቁባሽ
የነሙንጣዝ ኑሮ ሲመሽ
ከደም ጉማ ሮጦ ሲሸሽ
ቤተ መቅደስ ገብቶ ይምነሸነሽ?
ሌሎችን አደናበሮ
ዩኒፎርሙን ቀይሮ
አንዴ እንደ  ጸጋዬ  ቢራቢሮ
ወይ እንደ ጉድጓድ ከርከሮ
አንዴ እንደ ጫካ ቀበሮ
ደግሞ እንደ ገመሬ ዝንጀሮ
ከትላንት ተሰውሮ
ልብስና እምነት ቀይሮ
ሰታት ስለቆመ አቀርቅሮ
ለሱም ክፍት ነው በሩ?
እኮ እንዴት ነው ነገሩ?
አልገባኝም ምስጢሩ።

***
ወይም
እንደ ብርችምችም* እንደ ጠንፍየለሽ*
እንደ ሰናይት እንደ ብዙነሽ*
በልጅነት ዳንኪራ ደንካሪ
የአራዳዋ  ኮማሪ
ህይወት ሲሆንባት ቅራሪ
ትላንት ሆይ ሆይ
ዛሬ እማሆይ
መነኩሴ የደብሩ ዘማሪ
የገበዙ  ልዩ አማካሪ
አታመንዝሩን ደጋግመው የሰበሩ
በጭናቸው ወዝ የከበሩ  
ምነው እነሱ አልተነቀሉ?
ደግሞስ በስለት መልክ ከገቢያቸው ካቀበሉ
መንግስተ ሰማያትን ይወርሳሉ?

***
የሰው ነብሰ በላ በራሪ
ወይ የትላንቱ ቀላማጅ ቀባጣሪ
ዛሬ ሲሆን አስተማሪ
ተርጓሚና መስካሪ
የነብስ አባት አማካሪ 
ሲሆን የላይኛው ቤት አጋፋሪ
አባሆይ የአቡኑ አማካሪ
አይሆንም ወይ አነጋጋሪ?
እኮ እንዴት ነው ነገሩ?
አልገባኝም ምስጢሩ
ይበጃል መጠርጠሩ
ይህን አይልም መምህሩ።

***
ትላንት ባርያ ፈነገሉ
ዛሬ ለአምላክ አገለገሉ
በልጅነት ባሪያ ነገዱ
በመጻፉ ቀልድ ቀለዱ
ዛሬ በአምላክ ፍቅር አበዱ
ሀብት አፈሱ መዘበሩ
ትላንት በግፍ ከበሩ
ዛሬ ለአምላክ ዘመሩ
እኮ እንዴት ነው ነገሩ?
ለነሱም ክፍት ነው በሩ?
አልገባኝም ምስጢሩ።

ስበኩ አስተምሩ
በስሜ መስክሩ
በቃሌ ብርሀን ኑሮን ኑሩ
እንጅ…ሒዱና አደንቁሩ
ተቋም አቁሙ
ስዩም ሰይሙ
ተሸላለሙ
የልደት ስም ቀይሩ
ብሎአል ወይ መምህሩ?

እኮ እንዴት ነው ነገሩ?
መዋቅር ውቀሩ
ከቄሳር አብሩ
መድሎውን አታውሩ
ሂዱና አስገብሩ
ታጠቁ መዝብሩ
በስሜ አቅራሩ
በስሜ ፎክሩ
በስሜ አስፈራሩ
ደብር ደብሩ
ዕጣን አዙሩ
መሬት መዝብሩ 
ብሎአል ወይ መምህሩ?
ይበጃል መጠርጠሩ
ይህን አይልም መምህሩ። 

ምነው ምነው 

እንደ  ኦስካር ሮማርዮ እንደ ጉዲና ቱምሳ
እንደ ዴዝሞንድ ቱቱ  ወይም እንደ ፔጥሮስ መገርሳ dha
እንደ ዴኒስ ሀርሊይ 
እንደ ሚካዔል ላፕስሊይ
መድሎን የሚጻረር ለነብሱ የማይሳሳ
የቁርጥ ቀን ምዕመን ከዘመኑ ምዕመን አልገኝ አለሳ









መግለጫ
*ብርችምችም በጅማ  ጠንፍየለሽ፣ ሰናይት፣ እና ብዙነሽ በነቀምቴ ከተማ ኮማሪቶች ነበሩ

ዘለዓለም አበራ ተስፋ
                          14.10. 2019
                              ሔልሲንኪ  ፊንላንድ

Comments

  1. yaa'ee hin dhumu burqaan keessan. Safuu

    ReplyDelete
  2. Namtana,Rabbi ammallee arrabakee haaqaru.Dhugaa lafa jirtu,meshaa Oromoonkoo ittin cabe haqa lafa kesse,umrii dheeradhu.Kana hubachu dadhannee.Akka J.Keeniiyyaatta,jedhe,kitaaba nudura kahanii,yemmuu nutii ija cuufannee kadhannu isaan lafa kenya nurra fudhatu akkuma jedhe sana.Waantti kitaabichara jiruuf wantti maqaa amanttiichaatiin hojatamaa jiru faalaadha.kan nurratti duluun nucabseerra,kan amanttin nucabseetu irra caala.Jarri kaan qawwee qabatani nuwaraanani,isaan kuun + qabatani nuawwalani.Hori Bulii.

    ReplyDelete

Post a Comment

Popular posts from this blog

Geerarsaa: A Multifaceted Genre of the Oromoo Oral Art

Hooda Rirriittu eele / የማሰሻው ትንግርት

The Repertoires and Social Roles of Oromoo Asmaarii’s Performance